የኮሮናቫይረስ የዓለም ጤና ስጋት በሆነባቸው ባለፉት ወራት ወረርሽኙን በመፍራት በርካቶች በጣም አስፈላጊ ለሆኑ የቴና አገልግሎቶች ወደ ህክምና ተቋማት ከመሄድ እየተቆጠቡ መሆናቸው የጤና ባለሙያዎችን እያሳሰበ ነው። ከእነዚህም መካከል የእርግዝና ክትትል ለማግኘትና ለወሊድ ወደ ሐኪም ቤቶች መሄድ ያለባቸው እናቶች ስጋት ይጠቀሳል። ከእነዚህ ውስጥም ወ/ሮ መሠረት* ተመሳሳይ ስጋት ነበራት፤ ነገር ግን የሚጠበቅባትን ጥንቃቄ አድርጋ ከሳምንታት በፊት ሐኪም ቤት ውስጥ ወልዳለች። ነገር ግን ቀደም ሲል የምታውቃቸው ነገሮች በወረርሽኙ ምክንያት ተቀይሯል ስትል የገጠማትን ነገሮች ያሰፈረችበትን የግል ማስታወሻ ለቢቢሲ አጋርታለች።
ቀጥታ ዘገባ
የተጠቀሱት ሰዓቶቸ የዩናይትድ ኪንግደም ናቸዉ
ኮሮናቫይረስንና ኢምፔሪያሊዝምን 'እንደመስሳለን' ሲሉ የነበሩት ጆን ማጉፉሊ
ታንዛኒያዊው የፖለቲካ ተንታኝ ታቢት ጃኮብ ለቢቢሲ እንደተናገረው ማጉፉሊ ሥልጣኑን ሁሉ በእጃቸው አስገብተውም ቢሆን አንዳንድ ጊዜ የምዕራባዊያን ነገር ያባንናቸዋል። ብሔርተኝነታቸው መስመሩን ይስትና የሕዝበኝነት መስመርን ይይዛል።
ተጨማሪ ያንብቡበአዲስ አበባ ከተማ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 3434 ደረሰ
የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ማምሻውን ባወጣው መግለጫ በአዲስ አበባ ከተማ በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 3434 መድረሱን አስታወቀ።
ባለፉት 24 ሰዓታት 111 ሰዎች በኮቪድ-19 የተያዙ ሰዎች በአዲስ አበባ መገኘታቸውን የከተማዋ ጤና ቢሮ አስታወቋል፥
ከእነዚህ መካከል 92 ሰዎች የውጪ አገር የጉዞ ታሪክም ሆነ ቫይረሱ ካለበት ሰው ጋር ንክኪ የሌላቸው መሆናቸው ተገልጿል።
19 ሰዎች ቫይረሱ ካለበት ሰው ጋር ንክኪ ያላቸው እንዲሁም ሁለት ሰዎች የጉዞ ታሪክ ያላቸው መሆናቸውን የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ መግለጫ ያሳያል።
ከኮሮና ያገገሙት የ114 ዓመቱ አዛውንት ሕክምናቸውን ጨርሰው ቤታቸው ገቡ
ከኮሮናቫይረስ አገግመው ወደ የካቲት 12 ሆስፒታል ለተጨማሪ ሕክምና ተልከው የነበሩት የ114 ዓመት አዛውንት ሕክምናቸውን ጨርሰው መውጣታቸውን በየካቲት ሆስፒታል የውስጥ ደዌ ህክምና ስፔሻሊስት ዶ/ር ሊያ ፋንታሁን ለቢቢሲ ተናገሩ።
ተጨማሪ ያንብቡበአውሮፓ መመሪያዎች መላላታቸውን ተከትሎ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ከፍተኛ ጭማሬ አሳዬ
በባለፉት ወራት በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ መቀነስ ባሳየባት አውሮፓ ተጥለው የነበሩ ህጎች መላላታቸው ጋር ተያይዞ በሳምንቱ ውስጥ ከፍተኛ ጭማሬ ማሳየቱን የአለም ጤና ድርጅት አስታውቋል።
በአስራ አንድ ሃገራትም ውስጥ የቫይረሱ የማህበረሰብ ስርጭት የታየ ሲሆን ሌላ ዙር ወረርሽኝም ስጋት መደቀኑን የድርጅቱ የአውሮፓ ዳይሬክተር ዶክተር ሃኒስ ሄንሪ ክሎግ ተናግረዋል።
"ሃገራት ጥለውት የነበሩ መመሪያዎችን ማላላታቸውን ተከትሎ ሌላ ዙር ወረርሽኝ ሊከሰት እንደሚችል ሳስጠነቅቅ ነበር። በበርካታ አውሮፓ ሃገራትም ስጋቱ ወደ እውነታ መቀየሩ ነው" በማለት በዛሬው ዕለት በበይነ መረብ በነበረ የቪዲዮ ኮንፍረንስ ተናግረዋል።
በአውሮፓ 2.6 ሚሊዮን ሰዎች በቫይረሱ ሲያዙ 195 ሺህ ሰዎች ደግሞ በኮሮናቫይረስ ምክንያት ህይወታቸውን አጥተዋል። በአሁኑም ወቅት በአህጉሪቱ በቀን 20 ሺህ ሰዎች ያህል በቫይረሱ የሚያዙ ሲሆን ከ700 ያላነሱ ሰዎችም እንደሚሞቱ ተመዝግቧል።
በኢትዮጵያ ተጨማሪ 141 ሰዎች በኮሮናቫይረስ ሲያዙ የሶስት ሰዎች ህይወት አለፈ
የጤና ጥበቃ ሚኒስቴርና የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዛሬ ባወጡት መግለጫ ባለፉት 24 ሰዓታት በተደረገ 4675 የላብራቶሪምርመራም 141 ሰዎች በኮቪድ-19 መያዛቸው ተረጋግጧል።
በተጨማሪም ሶስት ሰዎች ሕይወታቸው ማለፉን መግለጫው አመልክቷል።
በአሁኑ ሰዓት በኢትዮጵያ 5175 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው በምርመራ ተረጋግጧል።
በኮሮናቫይረስ ጋር በተያያዘ መሞታቸው የተገለፁት ሶስት ሰዎች በጤና ተቋም ውስጥ በህክምና ላይ የነበሩ መሆናቸው ተገልጿል።
በአጠቃላይ በሀገራችን ቫይረሱ የተገኘባቸው እና ህይወታቸው ያለፈ ሰዎች ቁጥር 81 ደርሷል።
በተጨማሪም በትላንትናው ዕለት 58 ሰዎች ያገገሙ ሲሆን እነዚህም 44 ከአዲስ አበባ፣ ስምንት ከኦሮሚያ ክልል፣ ሶስት ከሶማሊ ክልል፣ ሁለት ከደደቡብ ክልል፣ እና አንድ ከትግራይ ክልል መሆናቸው ተገልጿል።
በአጠቃላይ ከኮሮናቫይረስ ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 1544 ደርሷል።
በአሜሪካ ተጨማሪ 1.4 ሚሊዮን ሰዎች ስራ ማጣታቸው ተገለፀ
በኮሮናቫይረስ ክፉኛ በተመታችው አሜሪካ በዚህ ሳምንት ተጨማሪ 1.4 ሚሊዮን ስራ ማጣታቸውን የአሜሪካ ሰራተኞች መስሪያ ቤት አስታውቋል።
በአሁኑ ሰዓት 19.5 ሚሊዮን አሜሪካውያን የስራ አጥ ጥቅማጥቅሞችን ከመንግሥት እያገኙ ነው ተብሏል።
የኮሮና ወረርሽኝ ከተከሰተበት መጋቢት አጋማሸ ጀምሮ የስራ አጡ ቁጥር በባለፉት ሳምንታት እየቀነሰ ነው ቢባልም አሁንም ቢሆን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ መሆናቸውም የሃገሪቱን ምጣኔ ኃብት ድቀት ውስጥ እየከተተው ነው።
በኮሮናቫይረስ በከፍተኛ ሁኔታ የተጠቃችው ኒውዮርክን ጨምሮ ሌሎች ግዛቶች ጥለዋቸው የነበሩ መመሪያዎችን በማንሳትም እንቅስቃሴዎችን ቢፈቅዱም የስራ አጡ ቁጥር አሁንም በሚሊዮኖች ነው።
ከእንቅስቃሴ ገደቡ ጋር ተያይዞ በኤርትራ የመሰረታዊ ሸቀጦች እጥረት አጋጠመ
በኤርትራ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ተከትሎ በተወሰዱ እርምጃዎች ምክንያት የመሰረታዊ ሸቀጦች እጥረት ማጋጠሙን፣ ገበያ ላይ ባሉት ሸቀጦችም ላይ የዋጋ ንረት በመታየቱ ለከፋ ችግር እየተጋለጡ መሆኑን ቢቢሲ ያናገራቸው ነዋሪዎች ገለጹ። በኤርትራ ቆላማ አካባቢዎች በተለይ በጋሽ ባርካ አካባቢ ሁኔታው የባሰ እንደሆነና በተለይም ሃይኮታ በሚባሉ የገጠር አካባቢዎች ህጻናት ለረሃብ እየተጋለጡ እንደሆነ የቢቢሲ ምንጮች ተናግረዋል።
ተጨማሪ ያንብቡታዋቂው የግላስቶንበሪ ፌስቲቫል ለሚቀጥለው አመት ደማቅ ፓርቲ ለማዘጋጀት ቃል ገባ
በሙዚቃውና የጥበቡ ዓለም ላይ ስመጥር የሆነው የእንግሊዙ ግላስቶንበሪ ፌስቲቫል የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ባይከሰት ኖሮ አምሳኛ አመት ክብረ በዓሉን በመጪው ቅዳሜና እሁድ ያከብር ነበር። ነገር ግን በርካታ ሁኔታዎችን ቀጥ ባደረገው ወረርሽኝ ምክንያት ከመከበር ተሰርዟል።
በዚህ ፌስቲቫል ላይ የኢትዮ ጃዝ ፈጣሪ ሙላቱ አስታጥቄን ጨምሮ በርካታ ታዋቂ ሙዚቀኞች የተሳተፉበትና ከመቶ ሺ በላይ የሚቆጠሩ የሙዚቃና የጥበብ ወዳጆች ከተለያዩ ሃገራት በመምጣት ለአምስት ቀናት ያህል ያለማቋረጥ ሙዚቃ የሚሰሙበት ስፍራ ነው።
የፌስቲቫሉ አዘጋጅ ኤሚሊ ኤቪስ ለቢቢሲ እንደተናገሩት በሚቀጥለው አመት ደማቅ ፓርቲ ለማዘጋጀት ቃል የገቡ ሲሆን በወረርሽኙ ማግስትም በህይወት መቆየትንም በሙዚቃ ለመዘከርም ታስቧል።
በዘንድሮው ፌስቲቫል ላይ ፓውል ማካርቲኒ፣ ቴይለር ስዊፍትና ኬንድሪክ ላማር ይዘፍናሉ ተብሎ የነበረ ሲሆን 200 ሺህ ተሳታፊዎችም ለመምጣት አቅደው ነበር።
የውሻ ፍቅር፡ "ጓደኛህን ሜዳ ላይ ትተኸው ልትሄድ አትችልም"
የውሻ ፍቅር፡ "ጓደኛህን ሜዳ ላይ ትተኸው ልትሄድ አትችልም"
በለንደን ባልተፈቀደ የመንገድ ላይ ድግስ ሰበብ 22 ፖሊሶች ተጎዱ
የለንደን ከተማ ፖሊስ 22 አባላቴ በመንገድ ላይ ድግስ ሰበብ ጉዳት ደርሶባቸዋል አለ።
ፖሊስ እንደሚለው አደጋው የደረሰው የወረርሽኝ ስጋት ባለበት በአሁኑ ወቅት ፖሊስ የመንገድ ላይ ድግስ ሊያዘጋጁ ያሰቡ ሰዎችን ሲበትን በተፈጠረ ግርግር ነው።
ከፖሊስ መኮንኖቹ አልፎ ተሽከርካሪዎችም ጉዳት እንደደረሰባቸው ፖሊስ አስታውቋል።
ሁለት ፖሊሶች ወደ ሆስፒታል የተወሰዱ ሲሆን አራት ሰዎች ደግሞ በቁጥጥር ሥር ውለዋል። ግሰለቦቹ የታሰሩት ያልተፈቀደ የመንገድ ላይ ድግስ በማዘጋጀታቸውና ግርግር በመፍጠራቸው ነው።
ብሪክስተን በተሰኘችው የለንደኗ መንደር ሊዘጋጅ የነበረውን ይህን ድግስ ሊያሰቆሙ የመጡ ፖሊሶችን ደጋሾቹ ሲያባሯቸውና መኪናዎችን ሲሰባብሩ የሚያሳዩ ተንቀሳቃሽ ምስሎች በማኅበራዊ መገናኛ መድረኮች ላይ ተሰራጭተዋል።
ዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ ሰብሰብ ብሎ ድግስ መደገስ ከኮሮናቫይረስ በኋላ ተከልክሏል። ቢሆንም በርካቶች ይህን ሕግ በመጣስ ሲደግሱ ይስተዋላሉ።
መምህራንና ወላጆች ትምህርት ቤቶች እንዲዘጉ ጠየቁ
በደቡብ አፍሪካዋ ዌስተርን ኬፕ ግዛት ያሉ መምህራንና ወላጆች መንግሥት ትምህር ቤቶችን እንዲዘጋ በማለት ተቃውሟቸውን በሰላማዊ ሰልፍ እያሰሙ ይገኛሉ።
መምህራኑና ወላጆች ት/ቤቶች እንዲዘጉ የጠየቁት በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ስጋት ነው።
የተወሰኑ ት/ቤቶች አስተዳዳሪዎች ለፕሬዝደንት ሲሪል ራማፎሳ ግልፅ ደብዳቤ ፅፈዋል። በደብዳቤው ላይ "ክቡር ፕሬዝደንት ሆይ እባክዎ ት/ቤቶችን ለመክፍት የወሰኑትን ውሳኔ ድጋሚ ያጢኑት" ሲሉ ተማፀነዋል።
ደብዳቤው፤ ወረርሽኙ ሕፃናት እንዲሁም መምህራንን እያዳረሰ በመሆኑ ትምህርት በቤቶቹ እንዲዘጉ ያሳስባል።
የዌስተርን ኬፕ ግዛት ትምህርት ክፍል እንዳወጣው መረጃ ከሆነ እስካሁን 300 መምህራንና አንድ ሕፃን በቫይረሱ ተይዘዋል።
አስተማሪዎች ቫይረሱ እንደተገኘባቸው ከተነገረ በኋላ አንዳንድ መምህራን ወደ ሥራ እንዳልመጡም ታውቋል።
ዌስተርን ኬፕ ደቡብ አፍሪካ በቫይረሱ እጅግ ከተጠቁ ግዛቶች ቀዳሚዋ ስትሆን በደቡብ አፍሪካ ቫይረሱ እንዳለባቸው ከታወቁ ሰዎች መካከል 50 በመቶዎቹ ይገኙባታል።
ወደ ባሕር ዳርቻዎች በሚጎርፈው ሕዝብ ምክንያት በሽታው እንዳያገረሽ ተሰግቷል
ዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው የበጋ ወቅትን ተከትሎ ሰዎች ለመዝናናት በብዛት ወደ ባሕር ዳርቻዎች መሄድ በመጀመራቸው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሊስፋፋ ይችላል የሚል ስጋት ተፈጥሯል።
ከተለያዩ ስፍራዎች በርካታ ሕዝብ በባሕር ዳርቻዎች ላይ ተሰባስቦ የሚያሳዩ ምስሎች የአገሪቱን የጤና ባለስልጣናትን አሳስቧል።
አንድ የደቡብ ምሥራቅ እንግሊዝ የፓርላማ አባል ሰዎች በመካከላቸው ሊኖር የሚገባውን የሁለት ሜትር አካላዊ እርቀት እንዲያከብሩ ጠይቀዋል።
አለዚያ ግን ወረርሽኙ ለሁለተኛ ጊዜ ሊያገረሽ እንደሚችል አስጠንቅቀው፤ ሰዎች ወደ ባሕር ዳርቻዎች ሲሄዱ የሚያደርጉትን ነገር በሙሉ ኃላፊነት በተሞላበት ሁኔታ በመፈጸም በሽታው ዳግም እንዳይከሰት እንዲያደርጉ መክረዋል።
የፓርላማ አባሉ በባሕር ዳርቻዎች አካባቢ ስተመለከቱት ነገር ሲናገሩ “እየሆነ ያለው ነገር ፍጹም ኃላፊነት የጎደለው ድርጊት ነው” ብለውታል።
ሌላ አንዲት የአካባቢው ባለስልጣንም ሕዝቡ ከሳምንት በኋላ ይከፈታሉ ተብለው የሚጠበቁት በባሕር ዳርቻው አካባቢ ያሉት የጎብኚዎች መዝናኛዎች እስኪከፈቱ ድረስ ከአካባቢው እንዲርቁ ጠይቀዋል።
ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ በወረርሽኙ ሰበብ የተዘጋው የፓሪስ ማማ ተከፈተ
የፈረንሳይ ዋና ከተማ ፓሪስ መለያ የሆነው የኤፍል ማማ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ለወራት ተዘግቶ ቆይቶ ተከፈተ።
ቢሆንም ግን ማማው ገና ወደ ቀድሞ ሥራው ሙሉ ለሙሉ እንደማይመለስ የተገለጸ ሲሆን ለጉብኝት የሚመጡ ሰዎች ቁጥር ውስን ከመሆኑ በተጨማሪ ከ11 ዓመት ዕድሜ በላይ ያሉ ሰዎች ጭምብል እንዲያደርጉ ይገደዳሉ።
ለአሁን ለጉብኙት ክፍት የሚሆኑት የማማው ክፍሎች አስከሁለተኛው ፎቅ ድረስ ያሉት ብቻ ሲሆኑ ቀሪው ክፍል ዝግ ሆኖ ይቆያል።
አስከ ሚቀጥለው ሳምንት ድረስ በማማው ላይ ያሉ አሳንሰሮች ስለማይሰሩ ፓሪስን ለመመልከት የሚፈልጉ ሰዎች ደረጃዎችን ብቻ መጠቀም እንዳለባቸው ተገልጿል።
የኤፍል ማማ ተሰርቶ የተጠናቀቀው በአውሮፓውያኑ በ1889 ነው። በዓመት ሰባት ሚሊዮን ሰዎች ይጎበኙት የነበረ ሲሆን ሦስት አራተኛ የሚሆኑት ሰዎች የሚመጡት ከሌሎች አገራት እንደሆነ ተነግሯል።
ከትራምፕ የደኅንነት አባላት መካከል የተወሰኑት የኮሮናቫይረስ ተገኘባቸው
ባለፈው ቅዳሜ ቱልሳ ውስጥ የተካሄደው የትራምፕ ምርጫ ቅስቀሳ ላይ የተገኙ የደኅንነት አባላት ለይቶ ማቆያ ገብተዋል። ይህ የሆነው ድግሞ ከመካከላቸው የተወሰኑት የኮሮናቫይረስ ስለተገኘባቸው ነው።
ዘገባውን መጀመሪያ ያወጣው ዋሽንግተን ፖስት ሲሆን ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ አንድ የፖሊስ ባለሥልጣን ደግሞ ለሲኤንኤን እንደተናገሩት በጣት የሚቆጠሩ አባላት ቫይረሱ ተገኝቶባቸዋል።
ከምርጫ ቅስቀሳው በፊት የፕሬዝደንት ትራምፕ የቅስቀሳ ቡድን አባላትና ሁለት የደኅንነት ሰዎችን ጨምሮ ስድስት ሰዎች ቫይረሱ እንደተገኘባቸው ተዘግቦ ነበር።
ፕሬዝደንት ትራምፕ፤ የኮሮናቫይረስ ስርጭት ባልተገታባት ኦክላሆማ ግዛት የምርጫ ቅስቀሳ አደርጋለሁ ሲሉ ብዙ ወቀሳ ገጥሟቸው ነበር።
በስብሰባው ቦታ የተገኙት ታዳሚዎችም ሙቀታቸው ተልክቶ እንዲሁም የእጅ ማፅጃ ፈሳሽ ተሰጥቷቸው ቢገቡም የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ ግዴታ አልነበረም።
የቅስቀሳ ቡድኑ አባላት አንድ ሚሊዮን ሰዎች ለመታደም ቃል ገብተዋል ብለው የነበረ ቢሆንም 19 ሺህ ሰው በሚይዘው ስታደየም የተገኙት 6200 ሰዎች ብቻ ነበሩ ተብሏል።
ኮቪድ-19 ያስተጓጎለው የኢትዮጵያ የካንሰር ህክምና
አዲስ አበባ ውስጥ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ ነው። የካንሰር ህሙማን ደግሞ ጥቁር አንበሳ ለሚያደርጉት ህክምና ወደ አዲስ አበባ መምጣት ግድ ስለሚላቸው አጣብቂኝ ውስጥ እንደገቡ ይናገራሉ። ሌላው ፈተና የህክምና ተቋማትና ባለሙያዎች አብዛኛውን ትኩረታቸውን ወደ ኮቪድ-19 ማድረጋቸው ነው።
ተጨማሪ ያንብቡየሴኔጋሉ ፕሬዝደንት ለ14 ቀናት ራሳቸውን አገገሉ
የሴኔጋሉ ፕሬዝደንት ኮሮናቫይረስ ከተገኘበት ሰው ጋር ንክኪ ስለነበራቸው ራሳቸውን ማግለላቸው ተነገረ።
ፕሬዝደንት ማኪ ሳል ለሚቀጥሉት ሁለት ሳምንት ራሳቸውን አግልለው የጤናቸውን ሁኔታ እንደሚከታተሉ ታውቋል።
ይህንን በተመለከተ ፕሬዝደንቱ አጠር ያለ መልዕክት ያስተላለፉት በአገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣብያ ቀርበው ነው።
ፕሬዝደንት ማኪ ለጊዜው ተመርምረው ነፃ ናቸው ቢባልም ከሁለት ሳምንት በኋላ ድጋሚ እንደሚመረመሩ ታውቋል።
የሴኔጋል ሕዝብ እንደራሴ የሆኑት ዬያ ዲያሎ ትላንት ረቡዕ ኮሮናቫይረስ እንዳለባቸው ማሳወቃቸው አይዘነጋም።
ሴኔጋል እስካሁን 6129 ሰዎች በቫይረሱ እንደተያዙባት አስታውቃለች። ከእኒዚህ መካከል 93 ሰዎች በቫይረሱ ምክንያት ለህልፈት ተዳርገዋል።
ተስፋ የተጣለበት የኮሮናቫይረስ ክትባት በሰዎች ላይ እየተሞከረ ነው
በሙከራ ላይ የሚገኘውና ትልቅ ተስፋ የተጣለበት የኮሮናቫይረስ ክትባት በዩናይትድ ኪንግደም በጎ ፈቃደኞች ላይ እየተሞከረ ነው። በሚቀጥሉት ሳምንታት ውስጥ ለ300 ሰዎች ላይ ይሰጣል የተባለውን ክትባት የሚመሩት ከኢምፔሪያል ኮሌጅ ሎንዶን ፕሮፌሰር ሮቢን ሻቶክ ናቸው። ክትባቱ በሰዎች ላይ ከመሞከሩ በፊት በእንሰሳት ላይ ተሞክሮ አበረታች ውጤት አሳይቷል። ክትባቱ ጉዳት እንደማያስከትልና ሰውነት የመከላከያ ሴሎችን እንዲያመርት እንደሚያነቃቃው በእንሰሳት ላይ በተደረገው ሙከራ ተረጋግጧል።
ተጨማሪ ያንብቡሕንድ በዓለም በአንድ ቀን ከፍተኛውን በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር አስመዘገበች
ሕንድ በአንድ ቀን 17 ሺህ ገደማ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን አስመዝግባለች። ይህም በዓለም እስከ ዛሬ ከታየው ከፍተኛው ነው ተብሏል።
በሕንድ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ470 ሺህ በላይ ሆኗል። 14 ሺህ 894 ሰዎች ደግሞ ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ ሕይወታቸውን አጥተዋል።
ዕለተ ረቡዕ ደለሂ 3788 በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች በማስመዝገብ በአገሪቱ ከፍተኛ ቁጥር ያለላቸው ህሙማን የተገኙባት ከተማ ሆናለች። እስካሁን ከ70 ሺህ በላይ ሰዎች ቫይረሱ እንዳለባቸው ተረጋግጧል። ከደልሂ ቀጥላ ሙምባይ ትገኛለች።
ደልሂ ውስጥ ቁጥር የጨመረው በርካታ ሰዎች እየተመረመሩ ስለሆነ ሊሆን ይችላል የሚል ግምት አለ። ከተማዋ ባለፈው ሳምንት ብቻ 100 ሺህ ገደማ ምርመራዎች አድርጋለች። በሕንዷ ዋና ከተማ እስካሁን 400 ሺህ ሰዎች ምርመራ ተደርጎላቸዋል።
የከተማዋ አስተዳዳሪዎች ነዋሪዎችን ቤት ለቤት እየሄዱ ፍተሻ ለማድረግ ዝግጅት ላይ ናቸው።
ከተማዋ በሕንድ ትልቁ ጊዜያዊ ሆስፒታል እየገነባች ትገኛለች። 10 ሺህ አልጋዎች እንደሚኖሩት የተነገረለት ይህ ሆስፒታል 22 የእግር ኳስ ሜዳዎችን ያክላል ተብሏል።
በዓለም ዙሪያ በቫይረሱ ከተያዙት መካከል ከግማሽ በላይ የሚሆኑት አገግመዋል
የኮሮናቫይረስ ወሬ ከተሰማበት ወርሃ ታኅሣሥ ጀምሮ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ በከፍተኛ ፍጥነት እየጨመረ ነው።
የኮሮናቫይረስ ኦፊሴላዊ መረጃዎችን የሚያወጣው ጆንስ ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ እንደሚያሳየው በአጠቃላይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ወደ 10 ሚሊዮን እየገሰገሰ ነው።
ዛሬ ሐሙስ ሰኔ 18/2012 አሃዙ ከ9.4 ሚሊዮን በላይ ሰዎች በቫይረሱ እንደተያዙ ያሳያል።
ከእነዚህ መካከል ግን ግማሽ ያህሉ ከቫይረሱ አገግመዋል። መላው ዓለም ከቫይረሱ ያገገሙ ሰዎች ቁጥር ከ4.7 ሚሊዮን በላይ ነው።
ብራዚል ውስጥ ከ660 ሺህ በላይ ሰዎች ሲያገግሙ በአሜሪካ ደግሞ ከ656 ሺህ በላይ ሰዎች መዳን ችለዋል። ሩሲያ 368 ሺህ፣ ሕንድ 258 ሺህ እና ቺሊ 215 ሺህ ሰዎች ከቫይረሱ እንዳገገሙ አስታውቀዋል።
ከአህጉረ አፍሪካ ደግሞ ደቡብ አፍሪካ ከ58 ሺህ በላይ ሰዎች ከቫይረሱ አገግመውባታል።
ኢትዮጵያ ደግሞ እስከ ትላንት ረቡዕ ሰኔ 17/2012 ድረስ 5034 ሰዎች በቫይረሱ እንደተያዙ ይፋ ስታደርግ ከእኒዚህ መካከል 1486 ሰዎች አገግመዋል።
ጨው ያዘለ ውሃ ለኮሮናቫይረስ መድኃኒትነት ሊሞከር ነው
ኤደንብራ ያሉ ሳይንቲስቶች ከፍተኛ የጨው መጠን ያለው ውሃ ለኮቪድ-19 መድኃኒት ሊሆን ይችል እንደሁ እየመረመሩ ነው።
ከዚህ በፊት በጉንፋን ላይ የተሠሩ ጥናቶች እንደሚያመለከቱት ጨዋማ ውሃ ተጠቅመው አፍንጫቸውን የሚያፀዱ ሰዎች ሳላቸው ቀለል ብሎላቸዋል በፍጥነትም ድነዋል።
ሳይንቲስቶቹ ስኮትላንድ ወስጥ ጥናቱ ላይ ለመሳተፍ ፈቃደኛ የሆኑ ሰዎችን እያፈላለጉ ናቸው። ተሳታፊዎች የበሽታው ምልክት ያለባቸው ወይም ደግሞ ቫይረሱ እንዳለባቸው የተረጋገጠ መሆን ይኖርባቸዋል።
አሁን ከሚደረገው ጥናት ቀደም ብሎ የተሠራው የሙከራ ጥናት ላይ ቀለል ያለ ጉንፋን ያለባቸው ሰዎች ጨዋማ ውሃ እንዲጠቀሙ ተደርገው ነበር።
ጨዋማ ውሃ የተጠቀሙት የጥናቱ ተሳታፊዎች ጉንፋኑ በአጭር ጊዜ ሲለቃቸው ወደ ሌላ ሰው የማስተላለፍ ዕድላቸውም ጠባብ ነበር ተብሏል። ከጉንፋን ለመዳን መድኃኒትም አላስፈለጋቸውም ይላል ቀደም ያለው ጥናት።
ፕሮፌሰር አዚዝ ሼይኽ አሁን ወደ ሙከራ ልንገባ ነው ይላሉ። ሙከራውን የምናደርገው ደግሞ ኮቪድ-19 ባለባቸው ወይም ምልክት በታየባቸው ሰዎች ላይ ነው፤ ውጤታማ እንደምንሆን ተስፋ አለኝ ይላሉ።
ጥናቱ ውጤታማ ከሆነ ከቫይረሱ የመዳን ፍጥነትን ሊጨምርና መስፋፋትን ሊቀንስ ይችላል።